Monday, December 16, 2013

የማለዳ ወግ … ስደተኛው ዘፋኝ በሳውዲ በርሃ …(ከጋዜጠኛ ነብዩ ሲራክ)

December 16, 2013የእንጀራ ነገር ሆኖብኝ እጓዛለሁ ፣ እጓዛለሁ ፣ እጓዛለሁ … እንደጨው ተበትነናልና ስፍር ቁጥር የሌላቸው ወገኖቸን በየሔድኩበት ከተማ ፣ እግር በጣለኝ የሳውዲ የቀለጡ በርሃዎች ወንድም እህቶቸን አገኛለሁ ። ላፍታም ቢሆን ጊዜ ሰጥቸ እየኑሩት ስላለው ኑሮ ፣ እየገፉት ስላለው ክፉም ደግ ተሞክሮ እጠይቃቸዋለሁ አንድም ሳይደብቁ የሆድ የሆዳቸውን ያጫውቱኛል …
እለተ ቅዳሜ በማለዳው ያቀናሁት በያንቦና በጅዳ መካከል በምትገኝ የዋዲ በርሃ ዙሪያ ነበር ። አየሩ ተቀያይሯል ፣ ከዚህ ቀደም ወደዚህ ቦታ ሳመራ እንደ እሳት ነበልባል የሚጋረፈው ሙቀት ዛሬ የለም ። ለስራ ወዳቀናሁበት በድቅድቁ በርሃ ላይ በተሰራው የድንጋይ መከስከሻ ፋብሪካ እንደደረስኩ አንድ መልከ መልካም ወንድም የግቢውን በር ከፍቶልኝ ለመግባት ወዴት መሄድ እንደምፈልግ የጠየቀኝ ወጣት ሃበሻ ለመሆኑ ቅንጣት ያህል አልተጠራጠርኩምና የሚጠይቀኝን ትቸ እኔው ጠየቅኩት “ሃበሻ ነህ! ” ነበር ያልኩ ። ይህን ስጠይቀው እንደ መሽኮርመም እና እንደመሳቅ እያለ “አዎ ሃበሻ ነኝ ፣ ኢትዮጵያዊ! ” ሲል መለሰልኝ! ብዙ ሃበሾች አላችሁ? ስል ጥያቄየን ቀጠልኩ “አዎ አምስት ሃበሾች አለን! ” አለኝ ፈገግ እያለ … በአሻጋሪ መምጣቴን የሚጠብቅ የፋብሪካው ሃላፊ “አስገባው ፣ አስገባው! ” ሲል ፍልቅልቁ ወንድም ተደናግጦ በወራጅ ብረት እንደነገሩ የተዘጋውን የግቢ ብረት አጥር ከፍቶልን እኔና የስራ ባልደረባ ረዳቴ የፊሊፒን ዜጋው ግላዲ ወደ ግቢው ስንገባ በመስኮት በኩል አንገቴን ወጣ አድርጌ ስራየን ከዋውኘ እንደማገኘው ቃል ገብቸለት ወደ ውስጥ ገባሁ …Saudi Arabia, Nebyu Sirak
ሱዳኑ የፋብሪካ ሃላፊ ከድንጋዩ መፍጫ የቅርብ ርቀት ካለው ጋራጅ አጠገብ ከተሰራች ባለሁለትና ሶስት ዛኒጋባ ቆርቆሮ ቤት ወጥቶ ሞቅ ያለ ሰላምታ ሰጥቶ ተቀበለን ። ድንጋዩን እየከሰከሰ ጠጠር የሚያደርገው ፋብሪካ ነጭ አመድ ወደ ሰማይ እየተፋ የጓራል …ዲንጋው እየተፈጨ ጠጠር እየተሰራ መሆኑ ነው! የመንገድ መደልደያ ፣ የምንገድ መጥረጊያ እና የመንገድ ማለስለሻ ዳምጤ ከባባድ የኮንስትራክሽን መኪኖችን ጨምሮ ጥገና የሚያስፈልጋቸው መኪኖች ጋራጁን አጨናንቀውታል … ከጋራጁ ጀርባ ደግሞ እኛ መመርመር ያከብን የተሽከርካሪ ጎማ መአት ተከምሯል። …አምስት የተባሉትን ሃበሾች አግኝቸ እስካዎጋቸው ቋምጫለሁ …የፊት የፊቱን እያስቀረብኩ ለፊሊፒኑ አጋሬ ምን መስራት እንዳለበት በማሳወቅ ስራውን አጣድፊ ግን በአግባቡ መርምሬ እንደጨረስኩት ሌሎች ሁለት ሃበሾች ሃበሻ ወንድማቸው መምጣቴን ሰምተው ኖሮ በፈገግታ እየተፍለቀለቁ መጥተው ሰላምታ ተለዋዎጥን …
ሃበሻ ዝር በማይልበት በርሃ ያገኙኝን ወንድም እነርሱም ሊያስተናግዱ ሊያጫውቱኝ እንደቋመጡ አልጠፋኝም … በተንቀሳቃሽ ኮንቴነር በፋይዚት ግሩም ሆና የተሰራቸው ማረፊያ ቤት ከጋራጁ የቅርብ ርቀር ትገኛለች ። አቧራ የጎረሰውን እጀን ሳልተጠብ በበርሃው ወዳገኘኋቸው ወንድሞች ማረፊያ ቤት አመራሁ … ረመድ ረመድ እያልኩ ከመድረሴ ወንድሞቸ በደስታ እየተፍለቀለቁ ግማሽ መንገድ ላይ ተቀበሉኝ ! ጠባቧ ቤት ማረፊያ ቤት ብቻ እንዳልሆነች ከበር የተደረደሩትን ጫማዎች ስመለከት ገባኝና ጫማየን አውልቄ “ቤት ለእንቦሳ! ” ብየ ዘው ብየ ገባሁ… ቤቷ ጽድት ያለች ናት … ሶስት አልጋዎች በሶስቱ የቤቱ ማዕዘኖች ጥግ ይዘው ተዘርግተዋል ። የተቀበሉኝ ወንድሞቸ ሶስት ሲሆኑ ዘግየት ብሎ ሌላ ወንድም ገባ … አምስተኛው ወንድም የት እንዳለ ስጠይቅ እሱ ስራ ላይ እንደሆነ ገለጹልኝ። ሁላችንም የምናወራው ከአልጋዎች ላይ ተቀምጠን ነው ። እንደገባኝ ከሆነ አልጋዎች ይተኛባቸዋል ብቻ ሳይሆን በመቀመጫነት ያገለግላሉ! … ጫዎታችን ከመጀመራችን በፊት እጀን ለመታጠብ ውሃ ቢጤ ስጠይቅ ድምጹ ጎርነን ያለው “ሸዋንግዛው እባላለሁ!” ብሎ የተዋወቀኝ ወንድም በእጅ ከምትያዝ ማቀዝቀዣ ውሃ ይዞ ወደ ” በር ላይ ላስታጥብህ! ” ብሎ ግማሽ ጎኔን ከበሩበወጣ አድርጌ እንደነገሩ ጣቶችን ውሃ አስነካሁ ብል ይሻላል ፣ ብቻ ታጠብኩ ።

አይ አበሻ! አበሻና ልመና፦ አንድ (ፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም )

December 16, 2013በዓለም ሕዝቦች መሀከል ውድድር ቢደረግ ያለጥርጥር አበሻ አንደኛ ከሚወጣባቸው ነገሮች አንዱ ልመና ሳይሆን አይቀርም፤ ለአበሻ፣ ልመና የኑሮ ዘዴ ነው፤ እንዲያውም ከልመና ውጭ የሆነ ኢትዮጵያዊ ኑሮ የለም ለማለት የሚቻል ይመስለኛል፤ ስለዚህም ልመና ባህላዊ ጥበብ ሆኖአል፤ አንዳንድ አላዋቂዎች፣ አንዳንድ አዋቂዎችም አንዳንዴ እየተሳሳቱ ልመናን እንደነውር ይገልጹታል፤ ልመና ነውር አይደለም፤ ለጨዋ ልጆችማ አንዳንድ አጥንትን የሚያበላሽ ሥራ ከመሥራት ለምኖ መብላት ክብር ነው፤ ይህ ባህላዊ ጥበብ ያልገባቸው የድሬ ዳዋ ለማኞች ብቻ ናቸው፤ እጃቸውን እየዘረጉ ‹‹እስቲ አሥር ብር ስጠኝ!›› ይላሉ! በጫት ሞቅ ሲላቸው መቶ ብር ይጠይቃሉ፤ የድሬ ዳዋ ልመና መሆኑ ነው!
Prof. Mesfin Woldemariamየጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው፤ ቄሶቹ ምንም ይስበኩ በተግባር እንደሚታየው ጽድቅ የሚገኘው በልመና ነው እንጂ በሥራ አይደለም፤ ሥራኮ ለአበሻ ከእርግማን የመጣ ነው፤ አበሻ አልተረገመ፤ ታዲያ ለምን ብሎ ይሥራ! አሁን እንደሚሰማውና እንደሚመስለኝ አገዛዙም እንደተቀበለው የቻይና ሰዎችም እንደመሰከሩለት ከሥራ ጋር ጠብ አለው፤ ደግሞስ ለምን ይሥራ! ለአንድ እንጀራ? ለተራበ አብልተው ለመጽደቅ የሚፈልጉ ስንትና ስንት ሰዎች አሉ፤ ስለዚህም ደግ ሰዎች መጽውተው እንዲጸድቁ በግድ ለማኞች ያስፈልጋሉ፤ ለመጽደቅም መለመን ያስፈልጋል፤ ጸሎት ልመና መሆኑን አትርሱ፤ ስለዚህም ዋናውና ከፍተኛው ልመና ወደእግዚአብሔር ነው፤ ብልጦቹ እግዚአብሔርን የሚለምኑት ሥልጣን፣ ሀብትና ጉልበት ነው፤ አንድ ቀን ተነሥተው እግዚአብሔር ሥልጣን፣ ሀብትና ጉልበት እንደሰጣቸው ያውጃሉ፤ አውጀውም በሕዝብ ራስ ላይ ይወጣሉ፤ በራሱ ላይ ወጥተውም ይጨፍራሉ፤ ሰውን ከመሬቱ፣ መሬቱን ከሰው መለየት ይሳናቸዋል፤ ሰውን ከመሬቱ፣ መሬቱን ከሰው ያጣላሉ፤ እግዚአብሔር ለእናንተ ብቻ እንዴት ሰጣችሁ? እግዚአብሔር እኛን ለምን ነፈገን? ብሎ የሚጠይቃቸውን እየደበደቡና እያቃጠሉ፣ እየገረፉና እያራቆቱ በዝምታ እንዲገዛ ያደርጉታል፤ አልበቃው ካለም አካሉን ለውሻ ሰጥተው ነፍሱን ወደእግዚአብሔር ይወረውራሉ፤ እግዚአብሔር እየቆጠረ የማይመዘግብ ይመስላቸዋል፤ የጠጠረ ጉልበታቸው ዓይኖቻቸውን አውሮ፣ ኅሊናቸውን አፍኖ እግዚአብሔር በዕዳ እንደሚይዛቸውና በጥጋባቸው ያደሉትን መከራና ስቃይ፣ የወረደውን እንባና ደም ከነወለዱ እንደሚያስከፍላቸው መገንዘብ ያቅታቸዋል።
እግዚአብሔር ፍርዱን እስቲሰጥ ድረስ ሥልጣን፣ ሀብትና ጉልበት ተረክበናል የሚሉት የተለያዩ ስሞችን እየለጠፉ በተዋረድ የለማኞችን ሠራዊት ያደራጃሉ፤ ሕዝብ ሁሉ ከነዚህ የለማኞች ሠራዊት በአንዱ ውስጥ ለመግባት በፉክክር ይተላለቃል፤ ሠራዊቱ ውስጥ በመግባት የሚገኘው ጉርሻ ልጆቻቸውን እንኳን ከረሀብ የማያድን መሆኑን ሳይገነዘቡ መብታቸውን እያስረገጡ የሌሎችን መብት ለመርገጥ መሣሪያ ይሆናሉ፤ እነዚህ እንግዲህ ልመናን በማኅበረሰቡ ውስጥ ተክለው እየኮተኮቱ የሚያስፋፉት ናቸው፤ ልመናን ባህል የሚያደርጉት እነዚህ ናቸው፤ ልመናን ታሪካችን ያደረጉት እነዚህና ከነሱ የቀደሙት ገዢዎቻችን ናቸው።
በእኛ ባህል የራበውን በማብላት ጽድቅ ይገኛል፤ ስለዚህም ለምኖ መብላት ይቻላል፤ ስለዚህም ሰዎች መጽውተው እንዲጸድቁ በግድ ለማኞች ያስፈልጋሉ፤ እንግዲህ ለምነው እየበሉ መኖር ከተቻለና እግዚአብሔርን በመለመን ጽድቅ ከተገኘ፣ የመሬቱንና የሰማዩን ጣጣ በልመና መገላገል ከተቻለ ታዲያ ሥራ ለምን ያስፈልጋል! ለነገሩስ ሥራ በእርግማን የመጣ ነው፤ ስለዚህ የተረገሙት ሲሠሩ ያልተረገሙ የሚመስላቸው ይለምኑ፤ ለሌላው ዓለም ልመና የችግር ምልክት ነው፤ ለአበሻ ግን ልመና የጽድቅ ምልክት ነው፤ የጨዋ ልጅ፣ ማለት በልመና በሰዎች ላይ ሥልጣንን ከአግዚአብሔር አግኝቻለሁ ብሎ የሚያምን፣ አይሠራም፤ ቀን ቢጥለውም የጨዋ ልጅ በእጁ ሠርቶ ከሚበላ ለምኖ ቢበላ ይሻለዋል፤ ሆድ የተፈጥሮ ነው፤ ረሀብም የዕለት ከዕለት የተፈጥሮ ግዳጅ ነው፤ ስለዚህም ለአበሻ የተፈጥሮን ሆድና የተፈጥሮን ረሀብ በልመና መወጣት የተፈጥሮን ሥርዓት መከተል መስሎ ይታየዋል።
ሌላ ቀርቶ ተማሪ ለምኖ ካልበላ ትምህርት አይገባውም፤ ለተማሪ ሲሆን ልመና አይባልም፤ ቀፈፋ ነው፤ አበሻ በልመና ምን ይህል እንደተራቀቀ የሚያመለክተው ለተለያዩ ልመናዎች የተለያዩ ስሞች ማውጣቱ ነው፤ እንደተባለው ተማሪ ሲለምን ቀፈፋ ነው፤ በዘመናዊ ቋንቋ የትምህርት ታክስ ነው፤ ምግብ የሚቀርብበትን ሰዓት እየጠበቀ ከተፍ የሚለው ቀላዋጭ ነው፤ አብዛኛውን ጊዜ ለቀላዋጭ ቀላል ሰበብ የሚሆነው ቀላውጦ የሚያገኘው ወሬ ነው፤ ሌላም የልመና ዓይነት አለ፤ እርጥባን ይባላል፤ — ደርቄአለሁና አርጥቡኝ ማለት ነው! ‹ላሊበላዎች› የሚባሉት ለምነን ካልበላን እንቆመጣለን በማለት ልመናን የኑሮ መሠረት አድርገውታል፤ ሌላም የልመና ዘር አለ፤ ደጅ መጥናት ይባላል፤ ደጅ መጥናት ማለት ብርዱን ችሎና እንቅልፉን አቋርጦ በሌሊት እየተነሡ በመኳንንቱና በመሳፍንቱ፣ በንጉሡ፣ በንጉሠ ነገሥቱ ደጃፍ ላይ አጥር ወይም ዛፍ እየተደገፉ የተፈለገውም ሰው ብቅ ሲል በመሬት ላይ በመነጠፍ እጅ በመንሣት ፊት ለማስወጋት ለመታወቅና ለሹመት ለመታጨት የሚጠቅም የልመና ዘዴ ነው፡፡ በአበሻ አገር ሁሉም ነገር በልመና ነው፤ ምግብ በልመና፣ ትምህርት በልመና፣ መሬት በልመና፣ … በልመና፣ ግብር የሚከፈለው በልመና ነው፤ ሥልጣን የሚገኘው በልመና ነው፤ ንጉሥነትም የሚገኘው በልመና ነው፤ ባጭሩ ኑሮ ማለት ልመና ነው፤ ልመና ማለት ኑሮ ነው ።